About

Thursday, November 19, 2020

ህዳር 11 ቅድስት ሀና


ህዳር 11 ቅድስት ሀና

"ሐና" ማለት በዕብራይስጥኛው "የእግዚአብሔር ስጦታ" እንደ ማለት ነው። "ሐና፣ ዮሐና፣ ሐናንያ" የሚሉ የዕብራይስጥ ስሞች ትርጉማቸው ተወራራሽ ነው።

❇️የዚህችን ቅድስት እናት ክብሯን መናገር የሚችል የለም። እርሷ ሰማይና ምድርን ለፈጠረ ለእግዚአብሔር ወልድ በሥጋ አያቱ ተብላለችና። አንድም ለሰማይና ለምድር ንግሥት ለድንግል ማርያም ወላጅ እናቷ ናትና። 

❇️ከዓለም ሴቶች ሁሉ የቅድስት ሐና ማኅጸን እንደ ምን ይከብር! በፍጥረት ታሪክ ለመጀመሪያ ጊዜ ጥንተ አብሶ (የአዳም በደል) መተላለፍ የቀረው በማኅጸነ ሐና ውስጥ ነውና። (ለዚህ አንክሮ ይገባል!) ይስሐቅን የተሸከመ የሣራ ማኅጸን ቡሩክ ከተባለ የቅድስት ሐናማ እንደምን አይባል! ከፍጥረታት ሁሉ እግዚአብሔር ድንግል ማርያምን እንደ መረጠ ሁሉ ቅድስት ሐናንም ለአያትነት መርጧታል። 

❇️ቅድስት ሐና ትውልዷ፣ ነገዷ ከላይ ከቅዱስ አብርሃም፣ ከታች ደግሞ ከነገደ ካህናት ነው። ይሕስ እንደ ምን ነው ቢሉ፦ አብርሃም ይስሐቅን፣ ይስሐቅ ያዕቆብን፣ ያዕቆብ ደግሞ ሌዊንና አሥራ አንድ ወንድሞቹን ይወልዳል። ሌዊ ቀዓትን፣ ቀዓት እንበረምን፣ እንበረም አሮን ካህኑን ይወልዳሉ። ቅዱስ አሮን አልዓዛርን፣ አልዓዛር ፊንሐስን እያለ ትውልዱ እስከ ቴክታና በጥሪቃ ይወርዳል። 

❇️ቴክታና በጥሪቃም ልጅ በማጣት ኖረው የእንቦሳዎች፣ የፀሐይና የጨረቃን ምሥጢር ተመልክተው ሄኤሜንን ይወልዳሉ። ሄኤሜን ዴርዴን፣ ዴርዴ ቶናሕን፣ ቶናሕ ሲካርን፣ ሲካርም ሔርሜላን ይወልዳሉ። 

❇️ሔርሜላም ከክርስቶስ ልደት ዘጠና ዓመታት በፊት ማጣት ("ጣ" ጠብቆ ይነበብ) የሚባል ደግ ሰው ከካህናት ወገን አግብታ በስርዓተ ኦሪት ትኖር ነበር። እግዚአብሔር ለዚህች ደግ ሴት የተባረኩ ሦስት ሴቶች ልጆችን ሰጣት። የመጀመሪያዋን "ማርያም" አለቻት። 

❇️ይህቺውም የአረጋዊው ዮሴፍ ሚስትና የቅድስት ሰሎሜ ቡርክት እናት ናት። 
ሁለተኛዋን "ሶፍያ" አለቻት። እርሷም ቅድስት ኤልሳቤጥን (የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስን እናት) ወልዳለች። በመጨረሻ የወለዷትን ግን "ሐና" አሏት።

❇️ይህቺውም የፈጣሪ የሥጋ አያቱ፣ የድንግል ማርያምም እናቷ ትሆን ዘንድ የተመረጠችውና ስም አጠራሯ የከበረው ዛሬ የምናከብራት እናት ናት። 

❇️መጽሐፈ ስንክሳርን ስመለከት እንዲህ የሚል ዓረፍተ ነገር አየሁ። "ለዛቲ ቅድስት ኢያዕመርነ ገድላቲሃ ዘትገብሮን በኅቡዕ ከመ ንዝክሮን" ይላል። ትርጉሙም "የዚህችን ቅድስት ገድሏንና ትሩፋቷን እንዳንዘረዝር አላወቅነውም።" እንደ ማለት ነው። የሚገርመው አበው እንዲህ ያሉት ክብሯን መግለጹን አልጠግብ ብለው ነው። 

❇️እኛም በመጠናችን የብጽዕት ሐናን ሕይወት በአጭሩ ቀጥለን እንመልከት። ብጽዕት ሐና ወላጆቿ (ማጣትና ሔርሜላ) ከካህናት ወገን በመሆናቸው ልጆቻቸውን በጥንቃቄ በሥርዓተ ኦሪት እንዳሳደጉ ይታመናል። ቅድስት ሐናንም ለአቅመ ሔዋን እስክትደርስ ድረስ በሕጉ፣ በሥርዓቱ አሳድገዋታል። 

❇️በወቅቱ በፈቃደ እግዚአብሔር ትውልዱ ከነገደ ይሁዳ የሚሆን አንድ ደግ ሰው አጩላት። ይህ ሰው "ኢያቄም" ይባላል። 

❇️አንዳንዴም "ሳዶቅ" ወይም "ዮናኪር" እየተባለ ይጠራል። ቅዱስ ኢያቄም ማለት ክፉ ከአንደበቱ የማይወጣው፣ ምጽዋትን የሚወድ፣ አምላከ እስራኤልን በንጹሕ ልቡ የሚያመልክ ሰው ነበረ። እንደ ኦሪቱ ሥርዓት ሁለቱ (ኢያቄም ወሐና) ከተጋቡ በኋላ ቶሎ መውለድ አልቻሉም። 

❇️ይህ ደግሞ የወቅቱ ከባድ ፈተና ነው። በዘመድ የከበሩ፣ በጠባያቸው የተመሰገኑ፣ መልካምንም የሚሠሩ ሰዎች ልጅ ስለሌላቸው ብቻ "ኅጡአነ በረከት" እየተባሉ ከቤተ እግዚአብሔር ይገፉ፣ በአደባባይም ይነቀፉ ነበር። ምክንያቱም በብሉይ ኪዳን ልጅ አለመውለድ እንደ ኃጢአተኛ ያስቆጥር ነበር። ደግነቱ የወቅቱ ሊቀ ካህናት ቅዱስ ዘካርያስ (የመጥምቀ መለኮት ቅዱስ ዮሐንስ አባት) እንደ እነሱ ልጅ ያጣ በመሆኑ አብረው ይጽናኑ ነበር። 

❇️የሆነው ሆኖ እኒህ ቡሩካን ሰዎች አምላከ እስራኤልን ከመለመንና ከማመስገን በቀር ሌላ ትርፍ አልተገኘባቸውም። ምንም የሞላቸውና የደላቸው ባይሆኑም ደሃን ሳያጐርሱ አይበሉም ነበር። ቅድስት ሐናን ግን "ቢወልዷት እንጂ አትወልድ።" 
እያሉ ጐረቤቶቿ ይሳለቁባት ነበር። ከማልቀስ በቀር ደግሞ መልስ አልነበራትም። 

❇️አንድ ቀን ግን ርግቦች ከልጆቻቸው ጋር ሲጫወቱ ተመልክታ "ፈጣሪ ሆይ! የእንስሳትን ማኅጸን የምትከፍት ዕፅዋትንም ከባሕርያቸው እንዲያፈሩ የምታደርግ:: እውነትም ሐናን ድንጋይ አድርገህ ፈጥረሃታልን?" ስትል አለቀሰች። 
ቅዱስ ኢያቄምም ወደ ተራራ ወጥቶ ለአርባ ቀናት አለቀሰ፤ ተማለለ። ይህ ሲሆን ሁለቱም አርጅተው ነበር። ሐምሌ ሠላሳ ቀን ግን ነጭ ርግብ ሰባቱን ሰማያት ሰንጥቃ በማኅጸነ ሐና ስታድር አዩ። ደስ ብሏቸው ለሰባት ቀናት ሱባኤ ይዘው ቅድስት ሐና እመቤታችንን ነሐሴ ሰባት ቀን ጸነሰቻት። ይህም ለእነርሱም ለወገኖቻቸውም ታላቅ ተድላ ሆነ። ብጽዕት ሐና ግን ፈጣሪዋን ታከብረው ዘንድ በጐነትንና ንጽሕናን አበዛች። 

❇️ጸንሳ ሳለም ዕውራንን አበራች፤ ድውያንን ፈወሰች። የጦሊቅ ልጅ በሞተ ጊዜም እያለቀሰች ስትዞረው ጥላዋ ቢያርፍበት አፈፍ ብሎ ተነስቶ፦ "ሰላም ለኪ እሙ ለፀሐየ ጽድቅ" ብሎ ድንግል ማርያምን "ወሰላም ለኪ እምሔውቱ ለዘገብረ ሰማየ ወምድረ" ብሎ ቅድስት ሐናን አመስግኗል። ትርጉሙም ድንግልን "የፀሐየ ጽድቅ እናቱ" ሐናን "ሰማይና ምድርን ለፈጠረ አያቱ" ማለት ነው። 

❇️ይህንን ያዩ አይሁድ ቅድስት ሐናን ሊገድሉ ብዙ ጊዜ ሞክረዋል። ግን መልአከ ሰላም ቅዱስ ገብርኤል አልፈቀደላቸውም። ግንቦት ፩ ቀንም የሰማይና የምድር ንግሥትን ሊባኖስ ተራራ ላይ ወልዳ ሽሙጥን ከሁላችንም አራቀች። ስሟን "ማርያም - የአምላክ ስጦታ" ብለው ሰይመው ለሦስት ዓመታት አሳድገዋታል። የሚገርመው በሦስቱ ዓመታት ውስጥ ቅድስት ሐና ድንግል ማርያምን ከክንዷ አውርዳት አታውቅም ነበር። 

❇️አንድ ጊዜም መላእክት ወስደውባት ፍጹም አልቅሳለች። ኋላ ግን መልሰውላታል። ሌላኛው የሚደንቀው እግዚአብሔር የዓለም ውዱን ስጦታ እመ ብርሃንን ሰጣቸው። እነርሱም ይህችን ውድ ስጦታ ሳይሰስቱ ለፈጣሪ መለሱለት። "እምቅድሜክሙ አልቦ ወእምድኅሬክሙ አልቦ ከመዝ መስዋዕት ለእግዚአብሔር ዘወሃቦ።" እንዲል። ቅድስት ሐና ድንግል ወደ ቤተ መቅደስ ከገባች በኋላ የእናትነት ፍቅሯ እያገበራት ለአምስት ዓመታት እየተመላለሰች ትጐበኛት፤ ትስማት ነበር። 

❇️እመቤታችን ስምንት ዓመት በሞላት ጊዜ ግን የእግዚአብሔር ጥሪ ወደ ቅድስት ሐና ደረሰ። ከክርስቶስ ልደት ስምንት ዓመታት አስቀድማ ብጽዕት እናት ሐና በዚህች ቀን ዐረፈች። ትንሽ ቆይቶም ባለቤቷ ቅዱስ ኢያቄም ተከተላት እኛም ልጆቿ "ብጽዕት ሐና ብጽዓን ይገባሻል!" እያልን እናመስግናት። 

❇️ሊቃውንቱ ለእርሷ እንዲህ ብለዋልና፦ "ሰላም ለኪ ለጸሎተ ኩሉ ምዕራጋ ከመ አስካለ ወይን ዲበ ሐረጋ ሐና ብጽዕት ተፈስሒ እንበለ ንትጋ እስመ ረከብኪ ሞገሰ ወአድማዕኪ ጸጋ እምሔውተ አምላክ ትኩኒ በሥጋ።

❇️" (አርኬ) አምላከ ብጽዕት ሐና በምልጃዋ ከዘላለም እሳት ያድነን። 

❇️ጸጋ በረከቷንም ይክፈለን።

ስንክሳር

No comments:

Post a Comment

ታህሳስ 6 ሰማዕቷ ቅድስት አርሴማ

GEDELEKIDUSAN ታህሳስ 3 ቅድስት አርሴማ(ቅዳሴ ቤቷ) ✝እናታችን ቅድስት አርሴማን በምን እንመስላታለን? እርሷ በአድማስ ላይ ተቀምጦ እንደሚያበራ እንቁ ናትና ክብሯ ብዙ ነው።  ✝መድኃኒታችን ክር...