About

Saturday, November 21, 2020

ህዳር 13 አዕላፍት መላእክት


ህዳር 13 - አዕላፍ መላእክት

❇️እግዚአብሔር ቅዱሳን መላእክትን ሲፈጥራቸው በነገድ መቶ በክፍለ ነገድ አሥር አድርጓቸዋል። አቀማመጣቸውንም በሦስት ሰማያትና በአሥር ከተሞች (ዓለማት) አድርጓል። 

❇️መላእክት ያሉባቸው ከተሞች ከታች ወደ ላይ 'ኤረር፣ ራማና ኢዮር' ይባላሉ። አሥሩ ክፍለ ነገድ ደግሞ ከነ አለቆቻቸው ይህንን ይመስላሉ። 

፩.አጋእዝት (የቀድሞ አለቃቸው ሳጥናኤል ሲሆን አሁን የተረፉት በቅዱስ ሚካኤል ሥር ናቸው።) 

፪.ኪሩቤል (አለቃቸው ኪሩብ) 

፫.ሱራፌል (አለቃቸው ሱራፊ) 

፬.ኃይላት (አለቃቸው ሚካኤል) 

፭.አርባብ (አለቃቸው ገብርኤል) 

፮.መናብርት (አለቃቸው ሩፋኤል) 

፯.ሥልጣናት (አለቃቸው ሱርያል) 

፰.መኳንንት (አለቃቸው ሰዳካኤል) 

፱.ሊቃናት (አለቃቸው ሰላታኤል) 

፲.መላእክት (አለቃቸው አናንኤል) ናቸው። 

❇️ከእነዚህም አጋእዝት፣ ኪሩቤል፣ ሱራፌልና ኃይላት መኖሪያቸው በኢዮር (በሦስተኛው ሰማይ) ነው። አርባብ፣ መናብርትና ሥልጣናት ቤታቸው ራማ (ሁለተኛው ሰማይ) ነው። መኳንንት፣ ሊቃናትና መላእክት ደግሞ የሚኖሩት በኤረር (በአንደኛው) ሰማይ ነው። 

❇️መላእክት ተፈጥሯቸው እምኀበ አልቦ ኀበ ቦ ነው። አይራቡም፣ አይጠሙም፣ አይዋለዱም፣ አይሞቱም። ተፈጥሯቸውም ረቂቅ ነው። ተግባራቸው ዘወትር "ቅዱስ፣ ቅዱስ፣ ቅዱስ" እያሉ ፈጣሪያቸውን ማመስገን ነው። ምግባቸውም ይሔው ነው። ዕረፍት ብሎ ነገርን አያውቁም። "አኮቴቶሙ ዕረፍቶሙ፣ ወዕረፍቶሙ አኮቴቶሙ" እንዲል። በተጨማሪም መልአክ ማለት ተላላኪ (አገልጋይ) ነውና ከፈጣሪ ወደ ሰው ልጆች ለምሕረትም፣ ለመዓትም ይላካሉ። ምሕረትን ያወርዳሉ። ልመናን ያሳርጋሉ። ቅጡ ሲባሉም ይቀጣሉ። ስነ ፍጥረት (አራቱ ወቅቶች) እንዳይዛቡ ይጠብቃሉ። ዘወትርም ስለ ሰው ልጆች ያማልዳሉ። (ዘካ. ፩፥፲፪) ምሥጢርን ይገልጣሉ። (ዳን. ፱፥፳፩) ይረዳሉ። (ኢያ. ፭፥፲፫) እንዳንሰናከል ይጠብቃሉ። (መዝ. ፺፥፲፩) ያድናሉ። (መዝ. ፴፫፥፯) ስግደት ይገባቸዋል። (መሳ. ፲፫፥፳ ፣ ኢያ. ፭፥፲፫ ፣ ራዕ. ፳፪፥፰) በፍርድ ቀንም ኃጥአንን ከጻድቃን ይለያሉ። (ማቴ. ፳፭፥፴፩) በአጠቃላይ ለሰው ልጆች ሕይወትና ድኅነት ሲባል ከፈጣሪያቸው የተሰጣቸውን ትዕዛዝ ሲጠብቁና ፈቃዱን ሲፈጽሙ ይኖራሉ። ይህ ዕለት በሊቃውንት አንደበት "አእላፍ" እየተባለ ይጠራል። በሃይማኖት፣ በተልእኮትና በምስጋና የሚኖሩ ዘጠና ዘጠኙ ነገደ መላእክት በአንድ ላይ የሚከበሩበት ቀን ነው። ምንም እንኳን የጐንደሩን ፊት ሚካኤልን ጨምሮ በአንዳንድ አድባራት ታቦቱ ቢኖርም ሲያነግሡ ተመልክቼ አላውቅም። ሊቃውንቱ በማኅሌት፣ ካህናቱም በቅዳሴ እንደሚያከብሯቸው ግን ይታወቃል። ኅዳር ፲፫ ቀን ዓመታዊ በዓላቸው ነው ማለት በየወሩ በአሥራ ሦስት ወርኀዊ በዓላቸው መሆኑን ያሳያልና ዘወትር ልናስባቸው ይገባል። ቅዱስ መጽሐፍ ቅዱሳን መላእክትን በስምና በማዕረግ እንደሚነግረን ሁሉ በማኅበር (በትዕይንት) አገልግሎታቸውም ይነግረናል። ለምሳሌ፦ ያዕቆብ በረዥም መሰላል ሲወጡና ሲወርዱ ተመልክቷል። (ዘፍ. ፳፰፥፲፪) ኤልሳዕ ለግያዝ አሳይቶታል። (፪ነገ. ፮፥፲፯) ዳንኤል ተመልክቷል። (ዳን. ፯፥፲) በልደት ጊዜ በዝማሬ መገለጣቸውን ቅዱስ ሉቃስ ጽፏል። (ሉቃ. ፪፥፲፫) ዮሐንስ በራዕዩ አይቷቸዋል። (ራዕይ. ፭፥፲፩) ከዚህም በላይ በብዙ የመጻሕፍት ክፍል ተጠቅሰዋል። 

❇️ቅዱሳን መላእክተ ብርሃን፣ መንፈሳውያን፣ ሰባሕያን፣ መዘምራን፣ መተንብላን (አማላጆች) ተብለውም ይጠራሉና ያስቡን ዘንድ ልናስባቸው ይገባል። 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር

ስንክሳር

No comments:

Post a Comment

ታህሳስ 6 ሰማዕቷ ቅድስት አርሴማ

GEDELEKIDUSAN ታህሳስ 3 ቅድስት አርሴማ(ቅዳሴ ቤቷ) ✝እናታችን ቅድስት አርሴማን በምን እንመስላታለን? እርሷ በአድማስ ላይ ተቀምጦ እንደሚያበራ እንቁ ናትና ክብሯ ብዙ ነው።  ✝መድኃኒታችን ክር...