About

Sunday, November 22, 2020

ህዳር 14 አባ ዳንኤል


ህዳር 14 አባ ዳንኤል 

††† እንኳን ለጻድቃን ቅዱሳን አባ ዳንኤል ወአባ መርትያኖስ ዓመታዊ የዕረፍት በዓል በሰላም አደረሳችሁ፤ አደረሰን። †††

††† በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን! †††

††† አባ ዳንኤል ገዳማዊ †††

††† በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን አካባቢ በፋርስ (የአሁኗ ኢራን) ውስጥ ብዙ አስቸጋሪ ነገሥታት ተነስተው ነበር:: ከእነዚህ አንዱ የሆነው የዘመኑ መሪ ክርስቶስን የማያውቅ: መምለኬ ጣኦት የሆነና በጠንቅ ዋዮች ተከቦ የሚኖር ነበር::

❇️እግዚአብሔር ለሁሉም የጥሪ ቀን አለውና ለሕይወት ይጠራው ዘንድ ይህንን ንጉሥ በደዌ ጐበኘው:: የአምላክ ጥሪው አንዳንዴ እንደዚህ: አንዳንዴም እንዲያ ነውና:: ንጉሡ እንደ ታመመ ጠቢባነ ፋርስ ሊያድኑት ሞከሩ:: ግን አልቻሉም:: ሕመሙ እየባሰ ሒዶ ንጉሡ መጻጉዕ ሆነ::
በጊዜው ከመተተኞች ሁሉ በጣም የሚያቀርበው አንድ ጠንቅ-ዋይ በቤተ መንግስት አካባቢ ነበርና ንጉሡ አስጠራው:: "አድነኝ" አለው:: እንደማይችለው ሲያውቅ ዝም አለው:: ንጉሡ መልሶ "ስማ! በቤቴ ውስጥ ከብረህ: ገነህ: የበላሁትን በልተህ: የጠጣሁትን ጠጥተህ የምትኖረው ለዚህ ላትሆነኝ ነው?" ብሎ ተቆጣው::

❇️የንጉሡን ቁጣ ያየው መተተኛ እንደሚገድለው ባወቀ ጊዜ "ንጉሥ ሆይ! እኔኮ አታደርገውም ብዬ ነው እንጂ መድኃኒቱን አውቀዋለሁ:: "ኅሥሥ ሕጻነ ዘዋሕድ ለአቡሁ ወእሙ-ለእናት አባቱ አንድ የሆነ ሕጻን ፈልግ:: እናቱ አስራው አባቱ ይረደውና በደሙ ታጥበህ ትድናለህ" አለው::
መተተኛው እንዲህ ያለው: "ሲሆን ንጉሡ እንዲህ አያደርግም:: ካልሆነ ግን እንዲህ ዓይነት ወላጆች አይገኙም" ብሎ ነው:: ንጉሥ ግን ላስፈልግ ባለ ጊዜ የሚያጣው ነገር የለምና አንድ ልጅ ብቻ ያላቸው ርጉማን ወላጆችን አገኘ::
"1 ሺህ ወቄት ወርቅ ልስጣችሁ እና ልጃችሁን ሰውልኝ" ቢላቸው "እሺ" ብለው ወደ ንጉሡ አደባባይ ወጡ:: በዚያም ሕዝብ ተሰብስቦ: ንጉሡም በዙፋኑ ተቀምጦ ሳለ የ5 ዓመት ሕጻን ልጃቸውን ለገንዘብ ይሰውት ዘንድ ወላጆቹ ቀረቡ:: እናቱ አጥብቃ አሰረችው:: አባቱ ደግሞ ቢላውን አስሎ ቀረበ::
በዚያች ሰዓት ግን ሕጻኑ ወደ ሰማይ ዐይኑን አቅንቶ: እንባው እየፈሰሰ ሲጸልይ ከንፈሮቹ ይንቀሳቀሱ ነበርና ንጉሡ ተመልክቶ ልቡ ራራ:: "እንዳትነኩት" ሲልም ጮኾ ተናገረ:: "ፍቱት" ብሎ ሕጻኑን አስፈትቶ በዙፋኑ ፊት ጠየቀው::

❇️"ምን እያደረክ ነበር?" ቢለው "ለሕጻን ልጅ ጋሻዎቹ ወላጆቹ ናቸው:: በደል ሲያገኘኝ ወደ ወላጆቼ እንዳልጮህ ገዳዮቼ እነሱው ናቸው:: ወደ ዳኛም አቤት እንዳልል አስገዳዩ ዳኛው ራሱ ነው:: ስለዚህም ተስፋየ አንዱ አምላክ እግዚአብሔር ብቻ ነበርና ወደ እርሱ በልቤ ጮህኩ" ሲል መለሰለት:: በዚህ የተገረመው ንጉሡ 1ሺ ወቄት ወርቁን ከወላጆቹ ቀምቶ ለሕጻኑ ሰጥቶ በሰላም አሰናበተው::

❇️ራርቶ ሕጻኑን የፈታው ንጉሥ ሕመሙ ቢጠናበት "የዚህ ሕጻን አምላክ እኔንም እርዳኝ!" ሲል ጮኸ:: በዚህ ጊዜ ጩኸቱ ወደ መንበረ ጸባኦት ደረሰለት:: የእግዚአብሔር ድምጽም ወደ ታላቁ ገዳማዊ ሰው ወደ አባ ዳንኤል መጣ:: "ሒደህ ፈውሰው" አለው::

❇️አባ ዳንኤል ማለት በዘመኑ ከነበሩ ዓበይት ጻድቃን አንዱ ሲሆን መንኖ በርሃ ከገባባት ቀን ጀምሮ በፍጹም ተጸምዶ: በጾም: በጸሎትና በትሕርምት የኖረ አባት ነው:: በዚያች ሰዓትም ጻድቁ በደመና ተጭኖ ከበርሃ ብሔረ ፋርስ ደረሰ:: ከንጉሡም ጋር ተነጋገረ::
ንጉሡ "አድነኝ?" ቢለው "እንድትድን በእውነተኛው አምላክ ማመን አለብህ" አለው:: "ክርስቶስ አምላክ መሆኑን በምን አውቃለሁ?" ብሎ በመጠየቁ ጻድቁ በፊቱ ብዙ ተአምራትን በስመ ክርስቶስ አደረገለት::

❇️ንጉሡም በክርስቶስ አምኖ በተጠመቀ ሰዓት አካሉ ታድሶ: ከደዌው ድኖ ተነሳ:: ሠራዊቱና ሕዝቡም እንዲሁ ተጠመቁ:: አባ ዳንኤልም በደመና ወደ በርሃ ተመልሶ ከተጋድሎ በኋላ በዚህች ቀን ዐርፏል::
††† አባ መርትያኖስ †††
††† ይህ ቅዱስ ሰው የነበረው በዚያው በ4ኛው መቶ ክ/ዘመን ሲሆን በትውልዱ ሶርያዊ ነው:: ብዙ ጊዜም "መርትያኖስ ካልዕ" (ሁለተኛው) እየተባለ ይጠራል:: ምክንያቱም ቀዳማዊ መርትያኖስ (ታላቁ) ስላሉ ነው::
አባ መርትያኖስ በምድረ ሶርያ ከክርስቲያን ወላጆቹ ጋር አድጐ: የቀናውን የሃይማኖት ትምሕርት ተምሮ: በጐውን ጐዳና መርጧል:: ወቅቱ አርዮሳውያን የበዙበት በመሆኑ ወገኖቹን ይጠቅም ዘንድ ያስተምር ነበር::
በየሥፍራውም እየሔደ ውሉደ አርዮስ (መናፍቃንን) እየተከራከረ ምላሽ ያሳጣቸው ነበር:: በዚህ የተበሳጩ መናፍቃንም አንድ ቀን አሳቻ መንገድ ላይ ጠብቀው በበትር ደበደቡት:: በሞትና በሕይወት መካከልም ትተውት ሔዱ:: እነሱ በዚህ እናስተወዋለን መስሏቸው ነበር::
እርሱ ግን በእግዚአብሔር ኃይል ድኖ እንደ ገና በሰው ፊት ምላሽ አሳጥቶ አሳፈራቸው:: እነርሱም መንገድ ላይ ጠብቀው እየደበደቡ ጐተቱት:: ለብዙ ጊዜም ሲደበድቡት ወደ በርሃ ሸሸ:: በዚያም ገዳማዊ ሰው ሆኖ በጾምና በጸሎት ኖረ:: በዓቱንም በኤርትራ ባሕር ዳርቻ አካባቢ ባለች አንዲት በርሃ አደረገ::

❇️እርሱ ግን በእግዚአብሔር ኃይል ድኖ እንደ ገና በሰው ፊት ምላሽ አሳጥቶ አሳፈራቸው:: እነርሱም መንገድ ላይ ጠብቀው እየደበደቡ ጐተቱት:: ለብዙ ጊዜም ሲደበድቡት ወደ በርሃ ሸሸ:: በዚያም ገዳማዊ ሰው ሆኖ በጾምና በጸሎት ኖረ:: በዓቱንም በኤርትራ ባሕር ዳርቻ አካባቢ ባለች አንዲት በርሃ አደረገ::
እግዚአብሔር ግን ይህንን ሐዋርያዊ ሰው ይፈልገዋልና እንደ ገና ወደ ከተማ የሚመለስበትን ምክንያት ፈጠረ:: በዘመኑ የሃገሩ ጠራክያ ጳጳስ ዐርፎ "ማንን እንሹም" ብለው ሲጨነቁ ፈጣሪ ጻድቁን በኅሊናቸው ሳለባቸው:: እንደ ምንም ብለው ፈልገው አገኙትና አሥረው አምጥተው የጠራክያ ኤጲስ ቆጶስ አደረጉት::
አሁን ስብከተ ወንጌል ሠመረ:: ምክንያቱም አርዮሳውያኑ እርሱ የመንጋው እረኛ ነውና መንካት አይችሉም:: ቢያደርጉትም እጅግ ተወዳጅ ስለ ሆነ ጠቡ ከሕዝብ ጋር ነው:: በዚሁ መንገድ አባ መርትያኖስ ተጋድሎውን ሳይገታ በሠመረ ስብከቱ ብዙዎችን አሳምኖ ወደ መንጋው ቀላቀለ::
ከሠራቸው ብዙ ተአምራትም አንዱን እነሆ:-
*አንዴ ቅዱሱ መንገድ ሲሔድ ጭቅጭቅ ሰምቶ ቀረበ:: በቦታው የተጋደመ ሬሳ አለ:: "ምንድን ነው ችግሩ?" ቢላቸው የሟች ወገኖች ወደ አንድ ጐረምሳ እየጠቆሙ "አላስቀብር አለን" አሉት::

❇️ያንን ጐረምሳ "ለምን?" ቢለው "ብድር ነበረበትና ካልከፈሉኝ አይቀበርም" አለው:: ጻድቁ ፈጣሪውን ጠይቆ ጐረምሳው በአጋጣሚው ሊያታልል መፈለጉን ተረዳ:: "ልጄ! ተወው ይቀበር" ብሎ ቢለምነው "አይሆንም! ምን ታመጣለህ?" አለው::
ያን ጊዜ አባ መርትያኖስ ጸልዮ የሞተውን "በስመ እግዚአብሔር ተነስ" ሲል አዘዘው:: የሞተውም አፈፍ ብሎ ተነሳ:: በዚህ ጊዜ ያ ሐሰተኛ በድንጋጤ ወድቆ ሞተ:: ለዚህኛው በተዘጋጀው መቃብርም ላይ ቀበሩት:: ከሞት የተነሳው ግን በደስታ ከወገኖቹ ጋር ሔደ:: አባ መርትያኖስም ከዘመናት በኋላ በዚህች ቀን ዐርፏል::
††† አምላከ አበው ኃይለ ተአምሩን: ረድኤተ ምሕረቱን አያርቅብን:: ከአባቶቻችን በረከትም ይክፈለን::
††† ኅዳር 14 ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት
1.አባ ዳንኤል ገዳማዊ
2.አባ መርትያኖስ ካልዕ (ዘጠራክያ)
3.አባ ዮሐንስ ዘደብረ ቢዘን (ኤርትራ)
4.ቅድስት ደብረ ቀልሞን
††† ወርሐዊ በዓላት
1.አቡነ አረጋዊ (ዘሚካኤል)
2.አባ ስምዖን ገዳማዊ
3.አባ ዮሐንስ ጻድቅ
4.እናታችን ቅድስት ነሣሒት
5.ቅዱስ ፊልጶስ ሐዋርያ (ከ72ቱ አርድእት)
6.ቅዱስ ገብረ ክርስቶስ መርዓዊ
7.ቅዱስ ሙሴ መርዓዊ

††† "ለአንዱም በአንዱ መንፈስ የመፈወስ ስጦታ: ለአንዱም ተአምራትን ማድረግ: ለአንዱም ትንቢትን መናገር: ለአንዱም መናፍስትን መለየት: ለአንዱም በልዩ ዓይነት ልሳን መናገር: ለአንዱም በልሳኖች የተነገረውን መተርጐም ይሰጠዋል:: ይህን ሁሉ ግን ያ አንዱ መንፈስ እንደሚፈቅድ ለእያንዳንዱ ለብቻው እያካፈለ ያደርገዋል::" †††
(፩ቆሮ. ፲፪፥፱)

ዝክረ ቅዱሳን 

1 comment:

ታህሳስ 6 ሰማዕቷ ቅድስት አርሴማ

GEDELEKIDUSAN ታህሳስ 3 ቅድስት አርሴማ(ቅዳሴ ቤቷ) ✝እናታችን ቅድስት አርሴማን በምን እንመስላታለን? እርሷ በአድማስ ላይ ተቀምጦ እንደሚያበራ እንቁ ናትና ክብሯ ብዙ ነው።  ✝መድኃኒታችን ክር...