About

Tuesday, November 24, 2020

ህዳር 16 ቅዱስ አቡናፍር ገዳማዊ


ህዳር 16
ቅዱስ አቡናፍር ገዳማዊ

❇️ጻድቁ ተወልዶ ያደገው በአምስተኛው መቶ ክፍለ ዘመን በምድረ ግብጽ ነው። ወቅቱ ሥርዓተ መነኮሳት የሚጠበቅበት፣ አበው ባሕታውያን እንደ ሰማይ ከዋክብት በዝተው የደመቁበት ነበር።

❇️ታላቁ አቡናፍርም ከክርስቲያን ወላጆቹ ተወልዶ፣ በሥርዓት አድጎ፣ መጻሕፍትንም ተምሮ ገና በወጣትነቱ መንኗል። 

❇️ሥርዓተ መነኮሳትን ከአባ ኤስድሮስ ታላቁ አጥንቶ ገዳሙንና መምህሩን እየረዳ ለብዙ ዓመታት በጾምና በጸሎት ኑሯል።
መነኮሳቱ ስለ ትሕትናውና ስለ ታዛዥነቱ ፈጽመው ያከብሩት ነበር። ከዕለታት በአንዱ ቀን አረጋውያን መነኮሳት ጭው ባለ በርሃ ስለሚኖሩ ባሕታውያን ሲጨዋወቱ፣ ሲያደንቋቸውም ሰማ።

❇️እርሱ በዚያ ወቅት ባሕታውያን በበርሃ መኖራቸውን አያውቅም ነበርና ሒዶ መምህሩን አባ ኤስድሮስን ጠየቃቸው። እርሳቸውም "አዎ ልጄ! ከዚህ በጣም ርቅው፣ ንጽሕናቸውን ጠብቀው፣ ከሰውና ከኃጢአት ተለይተው የሚኖሩ ገዳማውያን አሉ።" አሉት።

❇️ቅዱስ አቡናፍር "በዚህ ካሉት መነኮሳትና በበርሃ ካሉት ማን ይበልጣል?" ቢላቸው "እነርሱ በጣም ይበልጣሉ። ዓለም እንኳ ከነ ክብሯ የእግራቸውን ሰኮና አታህልም።" አሉት። ይህንን የሰማው ቅዱስ አባ አቡናፍር ጊዜ አላጠፋም፤ ከመምህሩ ቡራኬ ተቀብሎ ወደ በርሃ ሔደ። ለብዙ ቀናት ከተጓዘ በኋላ አንድ ባሕታዊ አግኝቶ አብሯቸው ተቀመጠ። ከእርሳቸው ዘንድም ሥርዓተ ባሕታውያንን ተምሮ እንደገና ወደ ዋናው በርሃ ጉዞውን ቀጠለ።
ከብዙ ቀናት መንገድ በኋላም አንድ ሠፊ ሜዳ ላይ ደረሰ። አካባቢው የውኃ ጠብታ የማይገኝበት ይቅርና መጠለያ ዛፍ የሣር ዘር እንኳ የሌለበት ወይም በልሳነ አበው "ዋዕየ ፀሐይ የጸናበት፣ ልምላሜ ሣዕር የሌለበት፣ ነቅዐ ማይ የማይገኝበት" ቦታ ነበር። 

❇️በዚህ ቦታ ይቅርና የሰው ልጅ አራዊትም አይኖሩበትም።
ለአባ አቡናፍር ግን ተመራጭ ቦታ ነበር። ቅዱሳኑን ይህ አያሳስባቸውም። ምክንያቱም ለእነርሱ ምግባቸውም፣ ልብሳቸውም ፍቅረ ክርስቶስ ነውና።

❇️አባ አቡናፍር ወደ ፈጣሪ ጸለዩ። በእግዚአብሔር ቸርነት ከጎናቸው አንዲት ዘንባባ (በቀልት) በቀለች። ከእግራቸው ሥርም ጽሩይ ማይ (ንጹሕ ምንጭ) ፈለቀች።
ጻድቁ ተጋድሏቸውን ቀጠሉ፤ ዓመታት አለፉ። ልብሳቸውን ፀሐይና ብርድ ጨርሶት ቅጠል ለበሱ። በዚያ ቦታም የሰው ዘርን ሳያዩ ለስልሳ ዓመታት በተጋድሎ ኖሩ። የሚያርፉበት ጊዜ ሲደርስ እግዚአብሔር አባ በፍኑትዮስን (የባሕታውያንን ዜና የጻፈ አባት ነው።) ላከላቸው።
ቃለ እግዚአብሔርን እየተጨዋወቱ ሳለ የአባ አቡናፍር አካሉ ተለወጠ፤ እንደ እሳትም ነደደ።

❇️አባ በፍኑትዮስም ደነገጠ። ታላቁ ገዳማዊ ግን እጆቻቸውን ዘርግተው ጸለዩ፣ ሰገዱና አማተቡ። ነፍሳቸውም ከሥጋቸው በፍቅር ተለየች። ቅዱሳን መላእክትም በዝማሬና በማኅሌት አሳረጓት። የሚገርመው ደግሞ አባ በፍኑትዮስ ይህን ሲያይ ቆይቶ ዘወር ቢል ዛፏ ወድቃለች፤ ምንጯም ደርቃለች።
አምላከ ቅዱሳን ጸጋውን ክብሩን፣ አእምሮውን፣ ለብዎውን ያሳድርብን። ከወዳጆቹ በረከትም ያሳትፈን።
ኅዳር ፲፮ ቀን የሚከበሩ ዓመታዊ የቅዱሳን በዓላት

፩.ቅዱስ አኖሬዎስ ጻድቅ (ንጉሠ ሮም)

፪.አባ ዳንኤል ገዳማዊ

፫.ቅዱስ አውሎጊስ መነኮስ

፬.ቅድስት ጣጡስ ሰማዕት

፭.አባ አቡናፍር ገዳማዊ

፮.ቅዱስ ኪስጦስ ሰማዕት

፯.ቅዱስ ፊቅጦር ምዑዝ

፰.አባ ዮሐንስ መሐሪ
ወርኀዊ በዓላት

፩.ኪዳነ ምሕረት (የሰባቱ ኪዳናት ማሕተም)

፪.ቅድስት ኤልሳቤጥ (የመጥምቁ ዮሐንስ እናት)

፫.ቅዱስ ገብረ ማርያም ጻድቅ ንጉሠ ኢትዮጵያ

፬.ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌሉ ዘወርቅ
"ዓለምን ወይም በዓለም ያሉትን አትውደዱ። በዓለም ያለው ሁሉ እርሱም የሥጋ ምኞትና የዓይን አምሮት ስለ ገንዘብም መመካት ከዓለም ስለ ሆነ እንጂ ከአባት ስላልሆነ ማንም ዓለምን ቢወድ የአባት ፍቅር በእርሱ ውስጥ የለም። ዓለሙም ምኞቱም ያልፋሉ። የእግዚአብሔርን ፈቃድ የሚያደርግ ግን ለዘላለም ይኖራል።" (፩ዮሐ ፪፥፲፭-፲፯) 

ወስብሐት ለእግዚአብሔር
ስንክሳር 

No comments:

Post a Comment

ታህሳስ 6 ሰማዕቷ ቅድስት አርሴማ

GEDELEKIDUSAN ታህሳስ 3 ቅድስት አርሴማ(ቅዳሴ ቤቷ) ✝እናታችን ቅድስት አርሴማን በምን እንመስላታለን? እርሷ በአድማስ ላይ ተቀምጦ እንደሚያበራ እንቁ ናትና ክብሯ ብዙ ነው።  ✝መድኃኒታችን ክር...